ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይኤምኤፍ) ከኢትዮጵያ ጋር በ3.4 ቢሊዮን ዶላር የተራዘመ የብድር ፋሲሊቲ መርሃግብር በአራተኛው ግምገማ ላይ በባለሞያዎች ደረጃ ስምምነት ላይ መድረሱን አስታውቋል።
ይህ ስምምነት የአይኤምኤፍ ሥራ አስፈፃሚ ቦርድ ሲያጸድቀው፣ ቀጣዩ የ261 ሚሊዮን ዶላር ክፍያ ለኢትዮጵያ እንዲለቀቅ መንገድ ይከፍታል። ይህ ክፍያ ሲፈጸም በአጠቃላይ በፕሮግራሙ ስር ለኢትዮጵያ የተሰጠው የገንዘብ ድጋፍ ወደ 2.13 ቢሊዮን ዶላር ከፍ ይላል።
የገንዘብ ተቋሙ ባወጣው መግለጫ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት የጀመረውን የማክሮ ኢኮኖሚ ማረጋጋት እና የልማት ማሻሻያዎችን በመገምገም፣ “የተሃድሶውን ፍጥነት ማስቀጠል የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋትን ለማጠናከር እና በመካከለኛ ጊዜ ዕድገትንና ድህነትን ለመቀነስ ቁልፍ ይሆናል” የሚል አስተያየት ሰጥቷል።
ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ በሐምሌ 2024 የድጋፍ ብድሩን ስትይዝ፣ ከባድ የውጭ ዕዳ መልሶ የማዋቀር ሥራ ላይ ትገኛለች። አይኤምኤፍ ባወጣው ሪፖርት፣ በG20 የጋራ ማዕቀፍ ስር የዕዳ ዘላቂነትን ለመመለስ የሚደረጉ ጥረቶች እየገፉ መሆናቸውን ጠቁሟል።
ምንም እንኳን ኢትዮጵያ ከሁለትዮሽ አበዳሪዎች ጋር በመደበኛ ዕዳዋ ላይ ስምምነት ላይ ብትደርስም፣ ባለሀብቶች ከ1 ቢሊዮን ዶላር የዩሮቦንድ ጋር በተያያዘ በሚደረገው የዕዳ ቅናሽ መጠን ላይ አለመግባባት መኖሩ የሂደቱን መጓተት እንዳስከተለ ይታወቃል።
በአይኤምኤፍ የባለሞያዎች ቡድን መሪ በሆኑት በአልቫሮ ፒሪስ የሚመራው ቡድን ከጥቅምት 20 እስከ ህዳር 4 ቀን 2018 ዓ.ም. ድረስ በአዲስ አበባ በመገኘት፣ በአይኤምኤፍ የተራዘመ የብድር ፋሲሊቲ መርሃግብር ስር በአራተኛው ግምገማ ዙሪያ ውይይት ማድረጋቸው ይታወቃል። ይህ ተከትሎ ደግሞ ከህዳር 24 እስከ 26 ቀን 2018 ዓ.ም. የቀጠለው ዉይይት በአዲስ አበባ ተካሄዶ ነበር።
ሚስተር ፒሪስ እንደተናገሩት ፤ “የአይኤምኤፍ ባለሞያዎች ቡድን እና የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት በተራዘመ የብድር ፋሲሊቲ ስምምነት ስር በኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ ፕሮግራም በአራተኛው ግምገማ ላይ በባለሞያዎች ደረጃ ስምምነት ላይ ደርሰዋል። ስምምነቱ በሚቀጥሉት ሳምንታት የአይኤምኤፍ ማኔጅመንት እና ሥራ አስፈፃሚ ቦርድ ማጽደቅ ይጠበቅበታል።
የማሻሻያውን ፍጥነት ማስቀጠል የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋትን ለማጠናከር እና በመካከለኛ ጊዜ ዕድገትንና ድህነትን ለመቀነስ ቁልፍ ይሆናል ያሉት አልቫሮ የዋጋ ግሽበትን ለመግታት ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ መከተል ተገቢ እንደሆነ አፅንኦ ሰጥተዉ ተናግረዋል ።
የባለሞያዎች ቡድን ከአስተዳዳሪዎች ጋር ባለፈዉ ሳምንት በኢትዮጵያ በነበራቸዉ ቆይታ ከገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ፣ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካለኝ እና ሌሎች ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር ተገናኝቶ ውይይት ማድረጋቸው ይታወሳል።





