የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ጉባኤ፤ ለግማሽ ክፍለ ዘመን ያህል ሲሰራበት የቆየውንና ኋላ ቀር የሆነውን የእፅዋት ጥበቃና ኳራንታይን አዋጅ የሚያሻሽል አዲስ ረቂቅ አዋጅ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል።
ይህ አዲስ የጸደቀው አዋጅ ቁጥር 1400/2018 ሆኖ የሚመዘገብ ሲሆን፣ ዋነኛ ዓላማውም የሥነ ሕይወት ዕፅዋት ብልሽትንና ብክነትን መከላከል እንዲሁም ዘመናዊ የተባይ መከላከልና መቆጣጠር ሥርዓትን መዘርጋት ነው።
የዕፅዋት ጥበቃና ኳራንታይን አዋጅ ከ55 ዓመታት በፊት ወደ ሥራ የገባ በመሆኑ ለወቅታዊ ቁጥጥር አመቺ ባለመሆኑ መሻሻሉ የግድ መሆኑ ተገልጿል።
በምክር ቤቱ የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ባቀረበው ሪፖርት ላይ ሰፊ ውይይት የተደረገ ሲሆን፣ በአዲሱ አዋጅ መሠረት በዕፅዋት ላይ ጉዳት ያደረሰ ማንኛውም አካል ከ1 እስከ 5 ዓመት በሚደርስ እስራት እንዲቀጣ ተደንግጓል።
በተጨማሪም ተቆጣጣሪ አካላት የሕግ ጥሰት ሲፈፅሙ ወይም የጉቦ ተግባር ላይ ሲሰማሩ በቀጥታ በእስራት እንዲቀጡ መደረጉ ተገልጿል።
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ላሌ እንደገለጹት፤ አዋጁ ደረጃውን የጠበቀ የተባይ አሰሳና ቅኝት ለማድረግ እንዲሁም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የሀገሪቱን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ጉልህ ድርሻ ይኖረዋል።






