በኢትዮጵያ ቀዳሚ ከሆኑት የቢራ አምራቾች አንዱ የሆነው የሐበሻ ቢራ አክሲዮን ማኅበር፣ በኢንዱስትሪው ላይ የተጣለው የ40% ኤክሳይዝ ታክስ እና አዲሱ የዲጂታል ኤክሳይዝ ታክስ ስታምፕ አሠራር በኩባንያው የፋይናንስና የሥራ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ጫና እያሳደረ መሆኑን አስጠነቀቀ።
ኩባንያው እንደሚገልጸው፣ ይህ 40 በመቶ የታክስ ተመን ታክሱ ምርቱ ከፋብሪካ ቅጥር ግቢ በወጣ ቅጽበት የሚታሰብና የሚከፈል በመሆኑ፣ ተቋሙ ገና ምርቱን ለገበያ አቅርቦ ገቢ ሳያገኝ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ለመንግሥት እንዲያስረክብ ይገደዳል።
ይህ አሠራር በተለይ እንደ ሐበሻ ቢራ ላሉ በማስፋፊያና በከፍተኛ የሥራ ማስኬጃ ወጪ ውስጥ ላሉ ኩባንያዎች ትልቅ የፋይናንስ ጫና ፈጥሯል።
ከነባሩ የታክስ ጫና በተጨማሪ፣ መንግሥት የንግድ ቁጥጥርን ለማጥበቅ ያስተዋወቀው የዲጂታል ኤክሳይዝ ታክስ ስታምፕ ሥርዓት ለኢንዱስትሪው ሌላው ትልቅ ስጋት ሆኗል። ሐበሻ ቢራ እንደገለፀው ፤ ይህ ሥርዓት በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ውስጥ ብቻ ወደ 372.3 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የሚጠጋ ቀጥተኛ ወጪ ያስከትላል።
ከዚህ የገንዘብ መጠን ውስጥ 223 ሚሊዮን ዶላር የሚሆነው ለሥራ ማስኬጃ የሚውል ሲሆን፣ ይህም በአገሪቱ እጥረት ባለበትና በከፍተኛ ሁኔታ በሚፈለገው የውጭ ምንዛሬ የሚከፈል ነው።
ይህ ወጪ በምርቱ የመሸጫ ዋጋ ላይ የሚኖረው ተጽዕኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። “ይህ ሥርዓት የታክስ አሰባሰብን ለማዘመን የታለመ ቢሆንም፣ የሚጠይቀው ወጪ ግን የኢንዱስትሪውን አቅም የሚፈታተን ነው” ይላሉ የዘርፉ ባለሙያዎች።
የቢራ ኢንዱስትሪው ከኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖዎች በተጨማሪ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ጫናዎችም እየበረቱበት ይገኛሉ። በቅርብ ዓመታት ውስጥ በአልኮል መጠጥ ላይ የሚሰነዘሩ ትችቶች መጨመራቸው መንግሥት ጥብቅ ገዳቢ እርምጃዎችን እንዲወስድ አድርጎታል።
በመገናኛ ብዙኃንና በሕዝባዊ ቦታዎች ላይ የተጣለው የአልኮል ማስታወቂያ እገዳ፣ ኩባንያዎች አዳዲስ ምርቶቻቸውን ለደንበኞቻቸው እንዳያስተዋውቁና የምርት ስማቸውን (Brand) እንዳይገነቡ አግዷቸዋል።
ይህ እገዳ ኩባንያዎች ደንበኞቻቸውን ለማግኘት ይበልጥ ውድ የሆኑና አድካሚ የሆኑ የንግድ ማስተዋወቂያ ስልቶችን እንዲከተሉ አስገድዷቸዋል፣ ይህም ተጨማሪ ወጪን የሚጠይቅ ነው።
ኩባንያው የገበያ ተደራሽነቱን ለማስፋት በሚያደርገው ጥረት ውስጥ እንቅፋቶች እንዳሉበት የገለፀ ሲሆን እነሱም እንደ ጠላ፣ ጠጅ እና አረቄ ያሉ ባሕላዊ መጠጦች ናቸው። እነዚህ መጠጦች ምንም ዓይነት የኤክሳይዝ ታክስ የማይከፈልባቸውና በዝቅተኛ ዋጋ በየመንደሩ የሚገኙ በመሆናቸው፣ የታክስ ጫና ያለበትን የፋብሪካ ቢራ በዋጋ እንደሚገዳደሩት አስታውቋል።






