የካናዳው “አላይድ ጎልድ” ኩባንያ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሚገኘው የኩርሙክ የወርቅ ማዕድን ፕሮጀክት በመጪው ሚያዝያ ወር ስራ እንደሚጀምር አስታወቀ። ኩባንያው ፕሮጀክቱ በ2026 ሶስተኛ ሩብ ዓመት ውስጥ ሙሉ በሙሉ ወደ ምርት እንደሚሸጋገር የገለጸ ሲሆን፣ በየዓመቱ 290 ሺህ አውንስ ወርቅ ለማምረት አቅዷል።
የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ፒተር ማሮን እንደገለጹት፣ ኩባንያው ለፍለጋ ስራ በየዓመቱ 8 ሚሊዮን ዶላር የመደበ ሲሆን፣ በቀጣይ አምስት ዓመታት ውስጥ የወርቅ ክምችቱን ወደ 5 ሚሊዮን አውንስ ለማሳደግ እየሰራ ይገኛል።
ማዕድን ማውጫው ከሰፈራ መንደሮች ርቆ የሚገኝ በመሆኑ ምንም ዓይነት የህዝብ ማፈናቀል ስራ እንዳልተከናወነ የጠቀሱት ስራ አስፈጻሚው፣ ድርጅታቸው የአካባቢውን ነዋሪዎች በቅድሚያ ለመቅጠር ፖሊሲ ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልጸዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ኩባንያው በኢትዮጵያ ምርት ሊጀምር መሆኑን ተከትሎ የአክሲዮን ዋጋው ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ በአራት እጥፍ በማደግ ከፍተኛ ውጤት አስመዝግቧል።
አላይድ ጎልድ ከኢትዮጵያ በተጨማሪ በማሊ እና በኮትዲቯር ግዙፍ የወርቅ ማዕድን ማውጫዎች እንዳሉት ይታወቃል።






