በኢትዮጵያ ተግባራዊ እየተደረገ ካለው አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ማዕቀፍ ውስጥ ዋነኛው የሆነው የውጭ ምንዛሬ ተመን በገበያ እንዲወሰን የማድረግ ሂደት፣ አሁንም በተለያዩ መዋቅራዊ ችግሮች ሳቢያ ተግዳሮት እየገጠመው መሆኑ ተጠቆመ።
በተለይም በባንኮች እና በትይዩ ገበያ (ጥቁር ገበያ) መካከል ያለው የዋጋ ልዩነት በቅርብ ሳምንታት ውስጥ ወደ 13 በመቶ ከፍ ማለቱ ተመልክቷል።
የአለምአቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) እንዳስታወቀው፤ ከመስከረም እስከ ጥቅምት አጋማሽ ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ በይፋዊው የባንክ ተመን እና በጥቁር ገበያው መካከል ያለው ልዩነት ከ10 በመቶ በታች ወርዶ የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ላይ ግን ልዩነቱ በድጋሚ እያገረሸ መምጣቱን አመልክቷል።
ለዚህም እንደ ዋና ምክንያት የተቀመጠው፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ከፍተኛ መጠን ያለው የውጭ ምንዛሬን ከጨረታ ውጭ ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሸጡ ነዉ ያለዉ ድርጅቱ ይህም የምንዛሬ ተመኑ በገበያ ውስጥ ያለውን ትክክለኛ የፍላጎት እና የአቅርቦት ሁኔታ እንዳያንጸባርቅ አድርጎታል።
በተጨማሪም ብሔራዊ ባንክ በሚያካሂደው የውጭ ምንዛሬ ጨረታ ላይ ባንኮች ሊያገኙ የሚችሉት ድርሻ ላይ ገደብ መቀመጡ፣ ባንኮች ያላቸውን የምንዛሬ ፍላጎት በነፃነት እንዳያሟሉ እና ትክክለኛ የዋጋ ግኝት እንዳይኖር እንቅፋት ሆኗል።
ካፒታል ጋዜጣ ከ አይኤምኤፍ ሪፖርት ላይ እንደተመለከተው፤ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እንደ ሀገር ስትራቴጂካዊ የሆኑ የነዳጅ እና የማዳበሪያ ግዢዎችን በብቸኝነት እንዲሸፍን መደረጉ፣ በባንኩ ላይ ያለውን የውጭ ምንዛሬ እጥረት አሁንም በከፍተኛ ደረጃ እንዲቀጥል አድርጎታል።
የግል ባንኮች እነዚህን ግዙፍ ሀገራዊ ሸክሞች ለመጋራት ያላቸው ፍላጎት አነስተኛ መሆኑ፣ በንግድ ባንክ ላይ ያለውን ጫና ከማክበዱም በላይ በገበያው ላይ የምንዛሬ እጥረት እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል።
ምንም እንኳን በባንኮች መካከል የሚደረግ የምንዛሬ ግብይት የተጀመረ ቢሆንም፣ ሂደቱ አሁንም ቢሆን “እንደ አስፈላጊነቱ የሚከናወንና የተቀናጀ ባለመሆኑ፣ ባንኮች ያላቸውን ትርፍ የውጭ ምንዛሬ እርስ በርስ በብቃት እንዳያለዋውጡ አድርጓቸዋል።
የሀገሪቱ የወርቅ እና የቡና ኤክስፖርት ከፍተኛ እድገት እያሳየ ቢመጣም፣ በትይዩ ገበያ ላይ ያለው የዋጋ ልዩነት መስፋት በኢኮኖሚው ላይ የራሱ የሆነ አሉታዊ ተጽዕኖ ይኖረዋል ነዉ የተባለዉ።
በኢያሱ ዘካሪያስ





