የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ዛሬ የካቲት 14 ቀን 2018 ዓ.ም ባካሄደው ልዩ የውጭ ምንዛሬ ጨረታ፣ የአንድ የአሜሪካ ዶላር አማካይ የመሸጫ ዋጋ ካለፈው ሳምንት የ1.21 በመቶ ቅናሽ በማሳየት 153.25 ብር መውረዱን አስታውቋል።
ባንኩ ለዚህ ልዩ ጨረታ እጅግ ከፍተኛ የሆነ 500 ሚሊዮን ዶላር ለገበያ ያቀረበ ቢሆንም፣ የንግድ ባንኮች የጠየቁት መጠን ግን ካቀረበው በታች ሆኖ ተመዝግቧል።
ይህም ባለፉት ሳምንታት በገበያው ላይ ይታይ የነበረውን ከፍተኛ የምንዛሬ ፍላጎትና የዋጋ ጭማሪ የገታ ክስተት ሆኗል።
በዛሬው ልዩ ጨረታ ላይ በአጠቃላይ 30 ባንኮች የተሳተፉ ሲሆን፣ የቀረበው የፍላጎት መጠን 455.29 ሚሊዮን ዶላር ሆኖ ተመዝግቧል።
ይህም ብሔራዊ ባንክ ካቀረበው 500 ሚሊዮን ዶላር ውስጥ 91.1 በመቶው ብቻ ገዢ ማግኘቱን የሚያሳይ ሲሆን፣ ቀሪው 44.71 ሚሊዮን ዶላር ወይም 8.9 በመቶው ሳይሸጥ መቅረቱን ካፒታል ጋዜጣ ለመረዳት ችሏል።
በጨረታው የተሳተፉት ሁሉም 30 ባንኮች የጠየቁትን የውጭ ምንዛሬ ሙሉ በሙሉ ማግኘት የቻሉ ሲሆን፣ ይህም ካለፈው ማክሰኞ የካቲት 10 ቀን 2018 ዓ.ም ጨረታ ጋር ሲነፃፀር ከፍተኛ ልዩነት አለው።
በወቅቱ ከቀረቡት 31 ባንኮች መካከል 21ዱ ወይም 67.7 በመቶው ብቻ ነበሩ አሸናፊ መሆን የቻሉት።
የዛሬው የጨረታ ውጤት ካለፈው ሳምንት መደበኛ ጨረታ ጋር ሲነፃፀር በዋጋ ረገድም መጠነኛ መረጋጋት የታየበት ነው።
ባለፈው ማክሰኞ በተካሄደው 18ኛው ዙር ጨረታ ከፍተኛው የመግዣ ዋጋ 155.1299 ብር የነበረ ሲሆን፣ በዛሬው ዕለት ግን ወደ 154.00 ብር ዝቅ ብሏል። ይህም የ0.73 በመቶ ቅናሽ አሳይቷል።
በተመሳሳይ ዝቅተኛው የመቁረጫ ዋጋ ካለፈው ሳምንት 155.1010 ብር ወደ 152.0079 ብር ዝቅ ብሏል።
ይህም የምንዛሬ ገበያው ካለፈው ጥር 26 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ሲያሳይ የነበረውን ቀጣይነት ያለው የዋጋ ጭማሪ የሰበረ ሆኗል።
ብሔራዊ ባንክ ዛሬ ያካሄደው ይህ ልዩ ጨረታ ለገበያው ያቀረበው የገንዘብ መጠን ከቀዳሚው ሳምንት የ70 ሚሊዮን ዶላር አቅርቦት ጋር ሲነፃፀር በ614 በመቶ ብልጫ አለው።
ይህ ከፍተኛ የዶላር አቅርቦት በገበያው ውስጥ ያለውን የውጭ ምንዛሬ እጥረት ለመቅረፍና የጥቁር ገበያውን ጫና ለመቀነስ ያለመ መሆኑ ይታወቃል።
ባንኩ በቀጣይም በወጣው መርሃ-ግብር መሠረት መሰል የውጭ ምንዛሬ ጨረታዎችን ማካሄዱን እንደሚቀጥል በመግለጫው አረጋግጧል።





