የአፍሪካ ደሀና በጦርነት ክፉኛ የተጎዳችው ደቡብ ሱዳን፣ እ.ኤ.አ በ2026 የነዳጅ ምርት ወደ ቀድሞ ሁኔታው በመመለሱ ምክንያት በአህጉሪቱ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት የሚያስመዘግቡ አገራትን እንደምትመራ የዓለም ባንክ አስታወቀ።
የዓለም ባንክ ባወጣው የቅርብ ጊዜው የዓለም የኢኮኖሚ ዕድገት ትንበያ መሠረት፣ የአገሪቱ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት (GDP) በ2026 በ48.8 በመቶ ያድጋል ተብሎ ይጠበቃል።
ይህ ከፍተኛ ዕድገት የታቀደው አገሪቱ ባለፈው ዓመት ካጋጠማት የ23.8 በመቶ የኢኮኖሚ ማሽቆልቆል በኋላ መሆኑም ታውቋል።
ከፍተኛ የኢኮኖሚ ማገገም የተገኘው በሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች እንደሆነ ሪፖርቱ ያመላክታል። የመጀመሪያው በሱዳን በኩል የሚያልፈው የነዳጅ ማስተላለፊያ ቧንቧ በመጠገኑ የነዳጅ ምርት ወደ መደበኛ ሁኔታው መመለሱ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ከአምስት ዓመታት የኢኮኖሚ ውድቀት በኋላ በአገሪቱ ውስጥ ያለው የንግድና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች መረጋጋት ነው።
ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) በበኩሉ ደቡብ ሱዳን በተጠናቀቀዉ በ2025 በ27.2 በመቶ ዕድገት እንደምታሳይ በመተንበይ የዓለም ባንክን የብሩህ ተስፋ ትንበያ አረጋግጧል። የአገሪቱ መንግሥት ገቢ ከ90 በመቶ በላይ የሚመነጨው ነዳጅ ሽያጭ እንደመሆኑ፣ የቧንቧው ጥገና ለኢኮኖሚው ትልቅ ትንፋሽ ሆኗል።
ሪፖርቱ በ2026 ሌሎች የአፍሪካ አገራት ሊያስመዘግቡት የሚችሉትን ዕድገትም ይፋ አድርጓል። በዚህም መሠረት ጊኒ በ9.3 በመቶ፣ ሩዋንዳ በ7.2 በመቶ፣ ኢትዮጵያ በ7.1 በመቶ እንዲሁም ናይጄሪያ ባለፉት አሥር ዓመታት ያላየችውን ከፍተኛ ዕድገት እንደሚያስመዘግቡ ተተንብዮአል።
በተቃራኒው እንደ ደቡብ አፍሪካ ያሉ ትልልቅ ኢኮኖሚዎች የ1.4 በመቶ ዝቅተኛ ዕድገት እንደሚያሳዩ ተጠቁሟል።






