የኢትዮጵያ መንግሥት በጤናው ዘርፍ የሚያደርገውን የገንዘብ ድጋፍ ለማሳደግ እና በዜጎች ላይ የሚደርሰውን የሕክምና ወጪ ጫና ለመቀነስ፣ በአልኮል፣ በትምባሆ እና በስኳር በበለጸጉ መጠጦች ላይ የሚጣለውን የታክስ ገቢ ለጤናው ዘርፍ ድጎማ እንዲውል ለማድረግ ማቀዱ ተገለፀ።
“ናሽናል ኸልዝ ኮምፓክት” በተሰኘው የዓለም ባንክ ሪፖርት መሰረት፣ “የኃጢአት ታክስ” (Sin Tax) ተብለው በሚጠሩት በእነዚህ ምርቶች ላይ የሚጣለው የቀረጥ ጭማሪ በቀጥታ ወደ ጤናው ዘርፍ እንዲፈስ ይደረጋል።
ከዚህ የሚገኘው ገቢ በዋነኝነት ለማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድን ድጎማ የሚውል ሲሆን፣ ዓላማውም አነስተኛ ገቢ ያላቸው እና ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን የሕክምና ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ነው።
ይህ አሰራር ተግባራዊ መደረጉ በዜጎች ላይ የሚደርሰውን ከፍተኛ የፋይናንስ ጫና በእጅጉ እንደሚቀንሰው ይጠበቃል።
በአሁኑ ወቅት ታካሚዎች ለሕክምና አገልግሎት ከኪሳቸው የሚያወጡት ቀጥተኛ ወጪ 39 በመቶ የሚሸፍን ሲሆን፣ በመንግሥት ድጎማ እና በታክስ ገቢው ዕገዛ እ.ኤ.አ በ2030 ይህንን ወጪ ወደ 20 በመቶ ዝቅ ለማድረግ ታቅዷል።
በተመሳሳይ ጊዜ የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድን ሽፋንን አሁን ካለበት 50 በመቶ ወደ 75 በመቶ ለማሳደግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ይህ የታክስ ገቢ እንደ ዋነኛ የፋይናንስ ምንጭ ያገለግላል።
ከገንዘብ ማሰባሰቡ ባሻገር፣ ይህ ስትራቴጂ መንግሥት ለጤናው ዘርፍ የሚመድበውን በጀት ለማሳደግ ካለው ቁርጠኝነት ጋር የተያያዘ ነው።
ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ የነበረባትን የውጭ ዕርዳታ ጥገኝነት በግማሽ በመቀነስ የሀገር ውስጥ የሀብት አሰባሰብን ለማጠናከር እየሰራች ሲሆን፣ እስከ 2030 ድረስ አጠቃላይ የጤና ወጪን 8.3 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ አልማለች።
ይህ የታክስ ማሻሻያ ውጤታማ በሆነ መንገድ ከተተገበረ፣ ለጤናው ዘርፍ ዘላቂ የገንዘብ ምንጭ ከመሆኑ ባለፈ፣ ጎጂ የሆኑ ምርቶች በህብረተሰቡ ጤና ላይ የሚያደርሱትን ጉዳት ለመቀነስ እንደ ትልቅ መፍትሔ እንደሚቆጠር ሪፖርቱ አመልክቷል።





