የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እና የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም፣ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያን ከሁሉም ባንኮች የደንበኞች ሂሳብ ቁጥር ጋር የማጣመር ስራ በይፋ መጀመሩን አስታውቀዋል።
ይህ ውህደት የፋይናንስ ዘርፉን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ አንድ እርምጃ ወደፊት የሚያስኬድ ወሳኝ ምዕራፍ እንደሆነ ተመላክቷል።
የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ከሁሉም ባንኮች የደንበኞች ባንክ ሂሳብ ቁጥር ጋር የማጣመር (Harmonization) ስራ በይፋ መጀመሩን ተከትሎ፣ ባንኮች ቀደም ሲል ይጠቀሙበት የነበረውን VeriFayda 1 (old eKYC) ስርዓት ሙሉ በሙሉ ትተው ወደ ይበልጥ ዘመናዊ እና የተቀናጀው VeriFayda 2 እንዲሸጋገሩ ተወስኗል።
VeriFayda 2 በኢቲስዊች (EthSwitch) በኩል የሚቀርብ ሲሆን፣ ባንኮች አዲስ ሂሳብ ለመክፈት (New Account Opening) እንዲሁም ነባር ሂሳቦችን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር ለማስተሳሰር (Existing Account Harmonization) ይህንኑ አዲስ ስርዓት ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል።
ይህ የመረጃ ስርዓት ባንኮች የደንበኞቻቸውን ትክክለኛ እና ወቅታዊ መረጃ እንዲያገኙ ከማስቻሉም በላይ፣ በሀሰተኛ ማንነት የሚከስት የገንዘብ መጭበርበርን ለመከላከል እንደ ቁልፍ የዲጂታል መሰረተ ልማት ያገለግላል።
ለባንኮች ወደ VeriFayda 2 የማሸጋገሪያ የጊዜ ሰሌዳ ወጥቶ ህዳር 25 ቀን 2018 ዓ.ም. መሰራጨቱ ተመላክቷል።
የፕሮግራሙ እና የኢቲስዊች የቴክኖሎጂ ባለሞያዎች ባንኮች የማሸጋገር ሥራውን በተሳካ ሁኔታ እንዲያከናውኑ የቴክኒክ ድጋፍ እና ክትትል እያደረጉ ሲሆን፣ በቀጣይም ድጋፉ የሚቀጥል ይሆናል።
ከዚህ ጋር በተያያዘ የባንክ ደንበኞች እስከ መጋቢት 30 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ የባንክ ሂሳባቸውን ከፋይዳ መረጃ ጋር እንዲያጣምሩ ጥብቅ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል።
ይህንን ለማድረግ ደንበኞች ወደ ባንክ ቅርንጫፎቻቸው በአካል በመሄድ ወይም ባንኩ በሚያስቀምጠው አሰራር መሰረት ኦንላይን የፋይዳ ተለዋጭ ቁጥራቸውን (06 አUዝ-FAN Number) ማቅረብ ይጠበቅባቸዋል።
ሁለቱ ተቋማት እንዳስታወቁት ፤ ለፋይዳ ያልተመዘገቡ ደንበኞች ደግሞ በቅድሚያ በአቅራቢያቸው በሚያገኙት የፋይዳ ምዝገባ ጣቢያ መመዝገብ እንዳለባቸው ተገልጿል።




