መንግሥት ላለፉት አራት ዓመታት በነዳጅ ምርቶች ላይ ሲያደርግ የነበረውን ድጎማ በከፍተኛ ሁኔታ በመቀነስ፣ እስከ መጪው የካቲት 2018 ዓ.ም. መጨረሻ ድረስ ከድጎማ ሥርዓቱ ሙሉ በሙሉ እንደሚወጣ ካፒታል ያገኘዉ መረጃ አመልክቷል።
ይህ ውሳኔ መንግሥት ከዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት ጋር በገባው ቃል መሠረት የኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተግባራዊ ለማድረግ የወሰደው እርምጃ አካል መሆኑ ለመረዳት ችሏል።
ባለሥልጣናቱ በገቡት ቃል መሠረት በዚህኛው የታኅሣሥ ወር መጀመሪያ ላይ አዲስ የዋጋ ጭማሪ ተግባራዊ አድርገዋል። በዚህም መሠረት ለተጠቃሚዎች የሚቀርበው የናፍጣ ዋጋ በ11 በመቶ፣ የቤንዚን ዋጋ ደግሞ በ5 በመቶ እንዲጨምር ተደርጓል።
ይህ ጭማሪ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ከ2025 መጀመሪያ አንስቶ በነዳጅ ውጤቶች ላይ የተደረገውን አጠቃላይ የዋጋ ጭማሪ በከፍተኛ ሁኔታ አሳድጎታል። ባለፉት አሥራ ሁለት ወራት ውስጥ ብቻ የናፍጣ ዋጋ በ43 በመቶ፣ የቤንዚን ዋጋ ደግሞ በ42 በመቶ የዋጋ ጭማሪ የታየባቸው ሲሆን፣ ይህም ድጎማውን ደረጃ በደረጃ የማንሳቱ ሂደት ውጤት መሆኑን ካፒታል ጋዜጣ ተመልክቷል።
መንግሥት ከ2014 ዓ.ም. ጀምሮ በሀገር ውስጥ የነዳጅ ዋጋ ላይ ሲያደርግ የነበረውን ጥቅል ድጎማ በሂደት በመቀነስ እስከ ሰኔ 2016 ዓ.ም. መጨረሻ ድረስ ከድጎማ ሥርዓት ሙሉ በሙሉ ለመውጣት አቅዶ እንደነበር ይታወሳል።
ይሁን እንጂ ዝቅተኛው የኅብረተሰብ ክፍል ከኑሮ ውድነት ጫና እንዲጠበቅ በሚል መንግሥት ከሐምሌ 2016 ዓ.ም. ጀምሮ እንደገና ጥቅል ድጎማ ማድረግ ጀምሮ ነበር።
ይህ የድጎማ አሠራር ከጎረቤት አገራት ጋር ያለውን የነዳጅ ዋጋ ልዩነት ሰፊ እንዲሆን በማድረጉ፣ ኮንትሮባንድና ሕገ-ወጥ ግብይት እንዲስፋፋ በር መክፈቱ ተገልጿል። ይህም በሀገር ሀብት ላይ ከፍተኛ ብክነት ከማስከተሉም በላይ በመንግሥት በጀት ላይ ሊሸከሙት የማይችሉት ጫና መፍጠሩን ባለሥልጣናቱ ይገልጻሉ።
ከነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ጎን ለጎን፣ የኤሌክትሪክ ታሪፍ ማስተካከያም እየተተገበረ ይገኛል። በጥቅምት ወር 2025 (እ.ኤ.አ.) የተደረገው የኤሌክትሪክ ታሪፍ ጭማሪ በየሦስት ወሩ በሚደረገው የዘርፉ ማሻሻያ ዕቅድ መሠረት የተከናወነ ሲሆን፣ ይህም የኃይል አቅርቦት ተቋማት ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ ያለመ መሆኑ ታውቋል።
መንግሥት እስከ የካቲት 2026 (እ.ኤ.አ.) ድረስ የነዳጅ ድጎማን ሙሉ በሙሉ በማስቀረት፣ የሀገር ውስጥ የነዳጅ ግብይት በዓለም አቀፍ የገበያ ዋጋ መሠረት እንዲመራ ለማድረግ እየሠራ እንደሚገኝ ተገልጿል።
በኢያሱ ዘካሪያስ





