የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት እንዳስታወቀው ፤ የዋጋ ግሽበቱ በሐምሌ ወር 15.3 በመቶ ሆኖ ተመዝግቧል ይህም በሰኔ ወር 2018 ዓ.ም. ከነበረው 13.9 በመቶ ጋር ሲነጻጸር የ1.4 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል።
የአገልግሎቱ መረጃ እንደሚያሳየው ፣ በሐምሌ ወር 2018 ዓ.ም. የተመዘገበው አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት መጠን ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ከነበረው 13.7 በመቶ ጋር ሲወዳደርም ጭማሪ አሳይቷል።
በወሩ ውስጥ የታየው ይህ አጠቃላይ የዋጋ ንረት ግፊት በዋናነት በምግብ እና ምግብ ነክ ባልሆኑ ሸቀጦች ላይ በተመዘገበው ጭማሪ የተከሰተ መሆኑ ተመላክቷል።
ለሐምሌ ወር አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት መጨመር ከፍተኛውን ድርሻ የያዘው የምግብ እና አልኮል ያልሆኑ መጠጦች ዋጋ ግሽበት ሲሆን፣ በወሩ 15.7 በመቶ ደርሷል።
በዚህ የምግብ ምድብ ውስጥ እህል (13.6 በመቶ)፣ ስንዴ (21.6 በመቶ)፣ የወተት ተዋጽኦዎችና እንቁላል (18.9 በመቶ)፣ ፍራፍሬ (19.2 በመቶ)፣ ዘይት (20.34 በመቶ) እና ስኳር (39.4 በመቶ) በመቶኛ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይተዋል።
በሌላ በኩል ደግሞ ምግብ ነክ ያልሆኑ ሸቀጦች የዋጋ ግሽበት በሐምሌ ወር 14.8 በመቶ ሆኖ ተመዝግቧል። በዚህ ዘርፍ ትራንስፖርት 15.6 በመቶ፣ አልኮል መጠጦችና ትምባሆ 16.0 በመቶ፣ ምግብ ቤቶችና ሆቴሎች 15.6 በመቶ እንዲሁም ሌሎች እቃዎችና አገልግሎቶች 19.3 በመቶ ድርሻ እንዳላቸው ሪፖርቱ አክሎ ገልጿል።





