የትምህርት አዋኪ ድርጊቶችን የሚፈጽሙ ግለሰቦች እና ተቋማት እስከ 150,000 ብር ቅጣት በአዲሱ ደንብ ይጠብቃቸዋል
ትምህርት ሚኒስቴር በትምህርት ተቋማትና አካባቢያቸው የትምህርት አዋኪ ጉዳዮችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ያለመ አዲስ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ረቂቅ ደንብ ማውጣቱን አስታውቋል።
ይህ ደንብ ከኢትዮጵያውያን ወግና ልማድ ጋር ይቃረናሉ ተብለው የተለዩ የውጭ ባህላዊ ልማዶችን ጨምሮ፣ እየጨመረ የመጣውን አዋኪ ጉዳዮች ለመግታት ያለመ መሆኑ ተጠቁሟል።
የደንቡ ዋና ዓላማ በትምህርት ቤቶችና አካባቢ የሚስተዋሉ አዋኪ ጉዳዮችን በመከላከል፣ ሁለንተናዊ ስብዕናው የተሟላ፣ በመልካም ሥነ-ምግባር የታነፀና ግብረ-ገብነትን የተላበሰ ብቁ ትውልድ እንዲፈጠር ማስቻል ነው።
ደንቡ የኢትዮጵያውያንን ባህልና ወግ የሚቃረኑ ተብለው በግልጽ የተዘረዘሩ አሉታዊ መጤ ድርጊቶችንና ክብረ በዓላትን በትምህርት ቤቶችና አካባቢ መፈጸም ሙሉ በሙሉ ይከለክላል።
የሀገሪቷን ባህልና ወግ ይቃረናል ከተባሉት ድርጊቶች ዉስጥ Crazy Day፣ Gentle Day ፣ Olds Day፣ Valentine Day፣ Color Day፣ Pyjama Day የሚሉት ይገኙበታል።
ካፒታል የተመለከተዉ ይህ ረቂቅ ደንቡ ፤ ከባህላዊ ልማዶች በተጨማሪ፣ የተማሪዎችን ትምህርት እና ሁለንተናዊ እድገት ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ የተለያዩ እንቅስቃሴዎችና የንግድ ተቋማት ተከልክለዋል።
ትምባሆ (ሲጋራ፣ ሺሻ)፣ ጫት፣ አልኮል፣ የናርኮቲክ እና ሳይኮትሮፒክ ዝርያ ያላቸው አደገኛ ህገ ወጥ መድኃኒቶችና ሱስ አስያዥ ዕፆች በትምህርት ቤቶችና አካባቢ መገኘት፣ መጠቀም፣ መሸጥ፣ ማብቀል፣ ማምረት ወይም መለወጥ የተከለከለ መሆኑን አስታውቋል።
የአልኮል መሸጫና ማከፋፈያ ቤቶች፣ የሲጋራ መሸጫ ሱቆች፣ ሺሻ ቤቶች፣ ጫት መሸጫና መቃሚያ ቤቶች፣ ጭፈራ ቤቶች፣ ቁማር ቤቶች፣ የእንግዳ ማረፊያ ቤቶች እና የሰውነት መታሻ (ማሳጅ) ቤቶች በአዲሱ ደንብ ተከለክለዋል።
እንዲሁም ፊልም ማጫዎቻ ቤቶች፣ ፕሌይ ስቴሽን ቤቶች፣ ዲ.ኤስ.ቲቪ ቤቶች፣ ከረንቡላ ፑል፣ ጆተኒ፣ ቢንጎ እና የስፖርት ቁማር መጫወቻ ቤቶችም እገዳ ከተጣለባቸው ድርጊቶች መካከል ዉስጥ ተካተዋል።
በሌላ በኩል በመማር ማስተማሩ ላይ ተጽዕኖ የሚያደርጉ ድምጽ ጫጫታ፣ መጥፎ ጠረን የሚያወጡ ነገሮች፣ ደረቅና ፈሳሽ ቆሻሻ የመጣል ተግባራት፣ እንዲሁም ወፍጮ ቤቶች፣ ብረታ-ብረት ብየዳ ቤቶች፣ እንጨት መሰንጠቂያ ቤቶች፣ ጋራዥ ቤቶችና አውቶብስ ፌርማታዎች የተከለከሉ ናቸው።
በትምህርት ቤት ውስጥና አካባቢ ህጻናት ተማሪዎችን ለጉልበት ብዝበዛና ለህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር የማመቻቸት ሥራ፣ እንዲሁም ሞባይል፣ ታብሌትና ሌሎች ኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችን ከትምህርት ውጭ መጠቀም ተከልክሏል።
እነዚህን ክልከላዎች ለማስፈጸም፣ ደንቡ የትምህርት አዋኪ ጉዳዮች እና ለመልካም ሥነ-ምግባር ተቃራኒ የሆኑ ድርጊቶች ከትምህርት ቤት አጥር 500 ሜትር ርቀት ላይ እንዲገኙ ግዴታ ይጥላል።
ደንቡ ተግባራዊ ከመሆኑ በፊት ትክክለኛውን ርቀት ሳይጠብቁ የተከፈቱ ተቋማት ላይ የማስተካከያ ጊዜና የማካካሻ ጉዳይ በዝርዝር መመሪያ እንደሚወሰንም ተመላክቷል።
ደንቡ አፈጻጸሙን በበላይነት የሚከታተልና የሚያስተባብር በፌደራል ደረጃ የሚቋቋም ግብረ-ኃይል መቋቋሙን ካፒታል ተመልክቷል።
የግብረ-ኃይሉ ሰብሳቢ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሲሆኑ፣ ምክትል ሰብሳቢው የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ናቸው። አባላትም የንግድ፣ ፍትህ፣ ጤና፣ ሰላም እና ሌሎች ሚኒስቴሮች እንዲሁም የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር፣ የመምህራን ማህበርና የተማሪዎች ወላጆች ህብረት ፕሬዝዳንቶች ይገኙበታል።
ደንቡ የገቢ ምንጭ ለማግኘት በሚል የተከለከሉ ድርጊቶችን ለሚፈጽሙ ግለሰቦችና ድርጅቶች ከፍተኛ የገንዘብ ቅጣቶችና የመዝጋት እርምጃዎችን ይደነግጋል።
ይህን ተከትሎ የጫት መሸጫና መቃሚያ የከፈተ – 50,000 ብር ተቀጥቶ ቦታውን እንዲዘጋ ይደረጋል የተባለ ሲሆን የሺሻና ሲጋራ መሸጫና ማስጨሻ የከፈተ – 100,000 ብር ተቀጥቶ ቦታውን እንደሚዘጋ ተጠቁሟል።
በተመሳሳይ የማንኛውም ዓይነት ቁማር ቤት የከፈተ – 150,000 ብር ቅጣት እንደሚጠብቀው የገለፀዉ ሚኒስትሩ የትምህርት አዋኪ ጉዳዮችን ለሚፈጽሙ ንብረታቸውን የሚያከራዩ – 30,000 ብር ተቀጥተው የአከራይ ተከራይ ውሉ እንደሚሰረዝ አመልክቷል።





