የቡና ባንክ አክሲዮን ማህበር የዳይሬክተሮች ቦርድ የባንኩን የተከፈለ ካፒታል በ2022 ዓ.ም. መጨረሻ (እ.ኤ.አ 2030) ወደ 20 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ የሚያስችል ስትራቴጂካዊ ዕቅድ አዘጋጅቶ ለባለአክሲዮኖች ጠቅላላ ጉባዔ የውሳኔ ሃሳብ ሊያቀርብ መሆኑ ተገልጿል።
ይህ ዕቅድ ባንኩን በቀጣይ 5 ዓመታት ውስጥ በኢትዮጵያ ከሚገኙ ሦስት ቀዳሚ የፋይናንስ ተቋማት ተርታ ለማሰለፍ የሚያስችል ነው።
የቦርዱ የተከፈለ ካፒታል የማሳደጊያ ዕቅድ በመጪው ቅዳሜ ህዳር 13 ቀን 2018 ዓ.ም. በሚያደርገዉ 16ኛዉ የባለአክስዮኖች መደበኛና 7ኛዉ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ቀርቦ ይፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል።
ባንኩ ካፒታልን ማሳደግ ያስፈለገበት ዋነኛው ምክንያት፣ ዛሬ ካፒታልን ማሳደግ የሕግ ግዴታን የመወጣት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፣ የህልውና እና የላቀ ተወዳዳሪነት ጉዳይ መሆኑን መገንዘብ ነዉ ሲል ቦርዱ አስታውቋል።
በስትራቴጂክ እቅዱ ላይ ካፒታል ጋዜጣ ለመመልከት እንደቻለው ፤ ብሔራዊ ባንክ ከዚህ የሒሳብ ዓመት ጀምሮ ተግባራዊ እንዲሆን ያጸደቀውና ባንኮች ለሌሎች ስጋቶችም በቂ መተማመኛ የሚሆን ጠቅላላ ካፒታል እንዲይዙ የሚያስገድድ አዲስና ጥብቅ መመሪያ ባንኩ ካፒታሉን እንዲያሳድግ ያስፈለገበት ቀዳሚዉ ምክንያት እንደሆነ በዝርዝር አስቀምጧል።
በተጨማሪም መንግሥት የባንክ ዘርፉን ለውጭ ባንኮች ክፍት ማድረጉን ተከትሎ የሚመጣውን ከፍተኛ ውድድር መቋቋም ለመቻይ ይህ ዉሳኔ በእጅጉ አስፈላጊ መሆኑን አፅንኦት በመስጠት አብራርቷል።
ቦርዱ ፤ ባንኩ የረጅም ጊዜ ስትራቴጂካዊ ዕቅዱን ለማሳካት እና በተለይ የብድር አቅርቦት አቅሙን በዘላቂነት ለማስፋት የሚያስችል ጠንካራና አስተማማኝ የካፒታል መሰረት መገንባት ወሳኝ እንደሆነ ገልጿል።
የቡና ባንክ የአምስት ዓመት ስትራቴጂካዊ የካፒታል ማሳደጊያ ዕቅድ ፤ ደንበኞች የሚፈልጉትን ዘመናዊ እና ፈጣን የዲጂታል አገልግሎት ለመስጠት በቴክኖሎጂ ላይ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ እና በውጭ ምንዛሪ አሠራር ላይ የታየውን ለውጥ እና ሊኖር የሚችለውን የዋጋ መስተካከል ተፅዕኖ ለመቋቋም ጠንካራ ካፒታል መኖሩ ወሳኝ እንደሆነ አመልክቷል።
የዚህ ዕቅድ መጽደቅና መተግበር ለባለአክሲዮኖች የላቀ ጥቅም እንደሚሰጥ የገለፀው ቦርዱ ከነዚህም መካከል የባንኩ አጠቃላይ ትርፍ ከሚጨመረው የአክሲዮን ብዛት በበለጠ ፍጥነት እንዲያድግ በማድረግ በአንድ አክሲዮን የሚገኘው ትርፍ (EPS) በዘላቂነት እንዲያድግ ይረዳል ብሏል።
በተጨማሪም የተሻለ የትርፍ ድርሻ (DPS) እንዲከፈል ማስቻል እና ባንኩ በራሱ ጥንካሬ እንዲቆም ስለሚያደርገው ወደ ፊት ከመንግስት ወይም ከብሔራዊ ባንክ በሚመጣ ‘በግድ የመዋሃድ’ ጫና ስጋት ውስጥ እንዳይገባ መከላከል እንደሚቻል ለባለአክሲዮኑ የአዲሱን እቅድ ያለውን ፋይዳ አስረድቷል።
ባንኩ፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ያስቀመጠውን የ5 ቢሊዮን ብር የተከፈለ ካፒታል የማሟላት ግዴታ ከተሰጠው የጊዜ ገደብ አንድ ዓመት ቀድሞ ማሳካቱን አስታውቋል።
የቡና ባንክ የ 2016 በጀት ዓመት ሪፖርት እንደሚያመለክተው፣ የቡና ባንክ የተከፈለ ካፒታል በ549.2 ሚሊዮን ብር በማደግ አጠቃላይ 4.83 ቢሊዮን ብር ደርሶ ነበር።
እንደ ሪፖርቱ ከሆነ ከተመሰረተ 16 ዓመታትን ያስቆጠረው ባንኩ፣ ከ14,000 በላይ ባለአክሲዮኖችን ያሉት ሲሆን በመላው አገሪቱ በሚገኙ 474 ቅርንጫፎቹም ከ4,100 በላይ ቋሚ ሠራተኞችን በመቅጠር የስራ እድል መፍጠር መቻሉ ተመላክቷል።





