የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ለንግዱ ማኅበረሰብ የሚሰጠውን የሁለት ወሳኝ አገልግሎቶችን ማለትም የወጪ ንግድ ኮንትራት ምዝገባ እና የመላኪያ ፈቃድ አገልግሎት ከመጪዉ ሰኞ ከታህሳስ 06 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ወደ ኦንላይን (በበይነ መረብ) ሥርዓት ማዘመኑን አስታወቀ።
የንግድ ስርዓትና ላይሰንሲንግ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ የሆኑት አብዱልሀኪም ሙሉ እንዳስታወቁት፣ ይህ እርምጃ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ለንግዱ ማኅበረሰብ የሚያቀርባቸውን አገልግሎቶች በቴክኖሎጂ በማዘመን ረገድ የወሰደው ሌላ ወሳኝ ምዕራፍ ነው።
ቀደም ሲል በማኑዋል ሲሰጥ የነበረው ይህ አገልግሎት ወደ ኦንላይን ሥርዓት ሙሉ በሙሉ መሸጋገሩ የአገልግሎቱን ተደራሽነት ከፍ ያደርጋል ተብሏል።
አብዱልሀኪም እንዳብራሩት፣ ይህ አዲስ የተዘረጋው ሥርዓት ላኪዎች የሚፈልጉትን አገልግሎት ከሰው ንክኪ ነጻ በሆነ መልኩ ባሉበት ቦታ ሆነው እንዲያገኙ ያስችላል። ይህም የተገልጋዮችን ጊዜና ወጪ ከመቆጠብም በላይ አገልግሎቱን ዘመናዊና ፍትሐዊ ያደርገዋል።
ሚኒስትር ዴኤታው አክለውም መንግስት የተገልጋዮችን እርካታ ለማረጋገጥ መጠነ ሰፊ ማሻሻያዎችን እያደረገ መሆኑን ገልጸው፣ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ቴክኖሎጂን መሰረት ያደረጉና ወጪ ቆጣቢ እንዲሆኑ በትጋት እየሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
ይህን ተከትሎ የንግድ ለመጀመር ይወስድ የነበረው ጊዜ ከ32 ቀናት ወደ 5 ቀን ወርዷል የተባለ ሲሆን ለንግድ ሥራ አጀማመር ይወስድ የነበረው ሂደት ደግሞ ከ11 ደረጃዎች ወደ 4 ደረጃዎች ዝቅ ማድረግ መቻሉን ካፒታል ያገኘው መረጃ ያመለክታል።






