የክልል መንግስታት ተግባራዊ እንዲያደርጉት የተዘጋጀው አዲሱ የንብረት ታክስ ሞዴል አዋጅ፣ በሕግ ከታክስ ነጻ የተደረጉ ንብረቶችና ተቋማት ለማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች ማካካሻ የሚሆን “በታክስ ምትክ የሚደረግ መዋጮ” እንዲከፍሉ የሚያስገድድ ድንጋጌ ይፋ አደረገ።
ይህ ውሳኔ በከተሞች ውስጥ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ፍትሃዊ በሆነ መንገድ በሁሉም ተጠቃሚዎች እንዲደገፉ ለማድረግ ያለመ መሆኑ ተገልጿል።
በዚህ አዋጅ የተወሰኑ የህብረተሰብ ክፍሎችና ተቋማት ከቀጥተኛ የንብረት ታክስ ነጻ እንዲሆኑ ተደንግጓል። ሆኖም እነዚህ ተቋማት የሚገኙባቸው አካባቢዎች በከተማ አስተዳደሩ የሚከናወኑ እንደ መንገድ ጥገና፣ የፍሳሽ ማስወገጃ፣ የጎዳና መብራት፣ የጽዳትና የደህንነት አገልግሎቶች ተጠቃሚ በመሆናቸው፣ ለእነዚህ አገልግሎቶች ማካካሻ የሚሆን መዋጮ እንዲከፍሉ ተደንግጓል።
እንደ ገንዘብ ሚኒስትር ማብራሪያ ከሆነ፤ የሃይማኖት ተቋማት ለአምልኮና ለመካነ መቃብር የሚጠቀሙባቸው ንብረቶች፣ ለህብረተሰቡ ነጻ ማህበራዊ አገልግሎት የሚሰጡ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች፣ እንዲሁም የመንግሥት ቢሮዎችና ዲፕሎማቲክ ተቋማት የሚጠቀሙባቸው ንብረቶች ከታክስ ነጻ ቢሆኑም፣ እንደየአካባቢው ነባራዊ ሁኔታ “በታክስ ምትክ የሚደረግ መዋጮ” ሊጠየቁ ይችላሉ።
አዋጁ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ከታክስ ጫና ለመታደግ ግልጽ የሆኑ መስፈርቶችን ያስቀመጠ ሲሆን በዚህም፤ ዓመታዊ ገቢያቸው ከአገራዊ አማካይ የነፍስ ወከፍ ገቢ 50 በመቶ የማይበልጥ እና በማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ የተረጋገጠላቸው “ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ቤተሰቦች” ከታክስ ነጻ ይሆናሉ።
በተጨማሪም ዋጋቸው በከተማ አስተዳደሮች ከአንድ ሚሊዮን ብር፣ በማዘጋጃ ቤት ከተሞች ከ250 ሺህ ብር፣ እንዲሁም በታዳጊ ከተሞች ከ100 ሺህ ብር ያነሰ የመኖሪያ ቤቶችና የቦታ ማሻሻያዎች ከንብረት ታክስ ነጻ ተደርገዋል።
በታክስ ምትክ የሚደረገው መዋጮ መጠንና ዓይነት በክልሉ መስተዳድር ምክር ቤት በሚወጣ ደንብ የሚወሰን ሲሆን፣ አወሳሰኑም “ፍትሐዊ፣ ተገቢና ትርጉም ያለው” መሆን እንዳለበት ተደንግጓል።
በተጨማሪም የታክስ ነጻ መብት የተሰጣቸው አካላት በየዓመቱ የታክስ ዘመኑ ከመጠናቀቁ 60 ቀናት በፊት የዕድሳት ማመልከቻ ማቅረብ ይኖርባቸዋል። ንብረቱ ለተሰጠው ዓላማ መዋሉን የሚያረጋግጡ ደጋፊ ሰነዶችን ማቅረብ የማይችሉ ወይም የባለቤትነትና የጥቅም ለውጥ አድርገው ሪፖርት ያላደረጉ አካላት፣ የታክስ ነጻ መብታቸው ሊሰረዝ ወይም ሊታገድ እንደሚችል አዋጁ ያስጠነቅቃል።
ይህ የተገለፀዉ የገንዘብ ሚኒስቴር ከሰሞኑ በሀገሪቱ የሚገኙ ከተሞች የራሳቸውን ገቢ በማሳደግ ጥራት ያለው መሠረተ ልማትና ማህበራዊ አገልግሎት እንዲያቀርቡ የሚያስችል “የሞዴል የንብረት ታክስ አዋጅ” አዘጋጅቶ ለክልል መንግስታት መላኩን ባሳወቀበት ደብዳቤ ላይ ነዉ።
ሚኒስትሩ አህመድ ሺዴ ለክልሎች በላኩት ደብዳቤ ላይ እንደገለጹት፣ ይህ አዋጅ የከተማ አስተዳደሮች በየአካባቢያቸው የንብረት ታክስ እንዲጥሉ፣ እንዲሰበስቡና ለልማት እንዲጠቀሙ የሚያስችል ሕጋዊ ማዕቀፍ ይፈጥራል።
ይህም ፈጣን የከተሜነት መስፋፋትን ተከትሎ እያደገ የመጣውን የአገልግሎትና የመሠረተ ልማት ፍላጎት ለመመለስና የከተሞችን የፊስካል ነጻነት ለማረጋገጥ የተወሰደ ታሪካዊ እርምጃ መሆኑ ተመልክቷል።
በአዋጁ መሠረት “ንብረት” ተብለው የተለዩት በከተማ ቦታ ላይ የሚገኝ የሊዝ ይዞታ መብት፣ የነባር ይዞታ መጠቀሚያ መብት፣ ሕንፃ እና በቦታ ላይ የተደረጉ ማሻሻያዎች ናቸው። ታክሱ በየዓመቱ የሚከፈል ሲሆን፣ የታክሱ መጠን እንደ ከተሞቹ ደረጃና እንደ ንብረቱ ዓይነት ይወሰናል።
በከተማ ቦታ የመጠቀም መብት ላይ የሚጣለው ታክስ ከንብረቱ ግምታዊ ዋጋ ከ0.2% ያላነሰ እና ከ1.0% ያልበለጠ እንዲሆን ተደንግጓል። በተጨማሪም ለልማት ተሰጥተው ነገር ግን በሕጉ በተቀመጠው ጊዜ ውስጥ ሕንፃ ያልተገነባባቸው ወይም ጥቅም ላይ ያልዋሉ ቦታዎች ከፍተኛ ታክስ እንዲከፈልባቸው በማድረግ የመሬት ግምትን ለትርፍ የመጠቀም ተግባርን ለመከላከል ያለመ መሆኑ ካፒታል ጋዜጣ ተመልክቷል።
ክልሎች ይህንን ሞዴል አዋጅ ከየክልላቸው ነባራዊ ሁኔታ ጋር በማጣጣም በምክር ቤቶቻቸው አፅድቀው ወደ ትግበራ እንዲገቡ ሚኒስቴሩ ማሳሰቢያ ሰጥቷል።





