በኢትዮጵያ ደቡባዊና ምሥራቃዊ አካባቢዎች እንዲሁም በጎረቤት ሶማሊያና ኬንያ የተከሰተው የድርቅ አደጋ ወደ ከፋ ደረጃ ተሸጋግሯል። እ.ኤ.አ ከጥቅምት እስከ ታኅሣሥ 2025 ሊዘንብ ይገባ የነበረው ዝናብ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ በመክሸፉ፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች ለከፋ የምግብ እጥረትና ለኑሮ መቃወስ ተጋልጠዋል።
በኢትዮጵያ የሶማሌ ክልል ደቡባዊና ምሥራቃዊ ክፍሎች፣ እንዲሁም እንደ ቦረና እና ባሌ ያሉ አካባቢዎች ለሁለተኛ እና ለሦስተኛ ተከታታይ ወቅት የዝናብ እጥረት እያጋጠማቸው ይገኛል። እንደ ሪፖርቱ ገለጻ፣ በእነዚህ አካባቢዎች የጣለው የዝናብ መጠን ከመደበኛው በ70 በመቶ ያነሰ ሲሆን፣ ይህም ከ1973 ዓ.ም (1981) ወዲህ የታየ እጅግ ዝቅተኛው የዝናብ መጠን ሆኖ ተመዝግቧል።
ምንም እንኳን በመካከለኛውና በሰሜን የሀገሪቱ ክፍሎች የነበረው የ”መህር” አዝመራ መልካም የሚባል ቢሆንም፣ በደቡብ የሀገሪቱ ክፍሎች ያለው የ”ደይር/ሐጋያ” ዝናብ መክሸፍ በእንስሳት ሀብት ላይ የተመሰረተውን የነዋሪዎች ኑሮ ክፉኛ እየጎዳው ነው። በተለይም በምሥራቅ ሐረርጌ ቆላማ አካባቢዎች እጅግ አስከፊ የሆነ የምግብ ዋስትና እጥረት (IPC Phase 4) በ2026 መጀመሪያ ላይ ሊከሰት እንደሚችል ተተንብዮአል።
የምግብና እርሻ ድርጅት (ፋኦ) መረጃ እንደሚያሳየው፣ በኢትዮጵያ፣ ኬንያና ሶማሊያ አዋሳኝ በሆነው “የማንዴራ ትሪያንግል” አካባቢ እስከ 95 በመቶ የሚሆነው የግጦሽ መሬት በድርቅ ተመቷል።
ከወትሮው የተለየ ከፍተኛ ሙቀት ከዝናብ እጥረቱ ጋር ተዳምሮ የአፈር እርጥበት እንዲጠፋና ዕፅዋት እንዲደርቁ በማድረጉ፣ የእንስሳት መኖና ውኃ ለማግኘት የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል።
ይህም የእንስሳት አካል እንዲከሳና ለሞት እንዲጋለጡ እያደረገ ሲሆን፣ ለሕፃናት ዋነኛ የአመጋገብ ምንጭ የሆነው የወተት ምርትም ሙሉ በሙሉ እንዲቆም አድርጓል። ይህም በክልሉ የሚገኙ ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ሕፃናትን ለከፋ የአልሚ ምግብ እጥረት አጋልጧል።
ድርቁ ያስከተለው የውኃና የግጦሽ እጥረት መጠነ ሰፊ መፈናቀልን እያስከተለ ይገኛል። ከሶማሊያ ድርቅን ሸሽተው ወደ ኢትዮጵያ ጋሻሞ እና ቦክ ወረዳዎች የተሻገሩ ዜጎች ቁጥር ከ55,800 በላይ መድረሱ ተገልጿል። ይህ ፍልሰት ቀድሞውኑ ውስን በሆነው የኢትዮጵያ የአካባቢው መርጃ አቅም ላይ ተጨማሪ ጫና እየፈጠረ ይገኛል።
ከዚህም በተጨማሪ ሴቶችና ሕፃናት ውኃ ፍለጋ ረጅም ርቀት ለመጓዝ በመገደዳቸው ለጾታዊ ጥቃት የመጋለጥ እድላቸው መጨመሩንና በትምህርት ገበታቸው ላይም ከፍተኛ መስተጓጎል እየደረሰ መሆኑ ተጠቁሟል።
የረሃብና የተመጣጠነ ምግብ እጥረት የሥራ ቡድን ከሰሞኑ ባወጣዉ አሳሳቢ ሪፖርት፣ የ2026 ዓ.ም ድርቅ ወደ ሰብዓዊ ጥፋት እንዳይቀየር ዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡ አስቸኳይ ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርቧል። እስካሁን ለሰብዓዊ እርዳታ የተገኘው የገንዘብ መጠን ከሚያስፈልገው ውስጥ 24 በመቶ ብቻ መሆኑ ስጋቱን የከፋ ያደርገዋል።





