በኢትዮጵያ የቴሌኮም ዘርፍ ውስጥ ሁለተኛው ግዙፍ ኦፕሬተር በመሆን በከፍተኛ ፍጥነት እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ፣ በዳታ (ኢንተርኔት) ጥቅል አገልግሎቶቹ ላይ ከፍተኛ የዋጋ ማሻሻያ ማድረጉን ይፋ አደረገ። ኩባንያው ማሻሻያ ማድረጉን ቢገልጽም፣ ደንበኞች ግን የተደረገው ለውጥ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ መሆኑን በመጥቀስ ቅሬታቸውን እየገለጹ ይገኛሉ።
ካፒታል በተመለከተዉ ዝርዝር መረጃ መሠረት፣ በሳፋሪኮም ኢትዮጵያ የዳታ ጥቅል አገልግሎቶች ላይ ከታኅሣሥ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ የሆነ ከፍተኛ የዋጋ ማሻሻያ ተደርጓል። ይህ ለውጥ በዋናነት በአብዛኞቹ ጥቅሎች ላይ ከ20% እስከ 82% የሚደርስ የዋጋ ጭማሪ ያስከተለ ነዉ።
በአዲሱ የዋጋ ዝርዝር እንደሚያመለክተው ፣ ቀደም ሲል ደንበኞች በ250 ብር ያገኙት የነበረው የ10 ጂቢ (GB) ሳምንታዊ የዳታ ጥቅል አሁን ላይ ወደ 5.5 ጂቢ ዝቅ እንዲል ተደርጓል።
በዕለታዊ ጥቅሎች ላይ የ50% እና የ67% ጭማሪ የታየ ሲሆን፣ ቀድሞ በ5 ብር ይገኝ የነበረው 150 MB ወደ 100 MB ዝቅ ብሏል። በሳምንታዊ እና ወርሃዊ ጥቅሎች ላይም ተመሳሳይ ለውጦች ተደርገዋል፤ የ100 ብር የሳምንት ጥቅል የሚሰጠው የዳታ መጠን ከ3 GB ወደ 2 GB ዝቅ ማለቱ የ50% ጭማሪን አሳይቷል።
በተጨማሪም ያልተገደበ (Unlimited) የዳታ ጥቅሎች ላይ ከ20% እስከ 25% የሚደርስ የዋጋ ጭማሪ የተደረገ ሲሆን፣ የሩብ ዓመት እና የግማሽ ዓመት ጥቅሎችም በ21% አድገው በቅደም ተከተል 4,250 ብር እና 8,500 ብር መድረሱን ካፒታል ጋዜጣ ከዋጋ ዝርዝሩ ለመረዳት ችሏል።
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ለዚህ የዋጋ ማስተካከያ ዋነኛ ምክንያት አድርጎ የጠቀሰው፣ እየጨመረ የመጣውን የሥራ ማስኬጃ (Operating costs) እና የኢንቨስትመንት ወጪዎችን ነው።
ኩባንያው ትላንት ታህሳስ 14፤2018 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ “ለ12 ሚሊዮን ደንበኞቻችን አስተማማኝ እና ጥራቱን የጠበቀ የኮኔክቲቪቲ ተሞክሮን ለማቅረብ የምናደርገውን ጥረት ለመቀጠል ይህ ማስተካከያ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል” ብሏል። ይህ የዋጋ ጭማሪ በድንገት የመጣ እንዳልሆነም ይነገራል።
ካፒታል ጋዜጣ ከአምስት ወራት በፊት የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዊም ቫንሄለፑት ዋቢ አድርጎ እንደዘገበዉ ፤ በኩባንያው በአሁኑ ወቅት ያለው የሞባይል ዳታ የዋጋ ተመን ከወጪ በታች እየተሸጠ መሆኑንና ይህም የረጅም ጊዜ የቴሌኮም ዘርፉን ህልውና አደጋ ላይ እንደሚጥል ስጋታቸውን ገልፀዋል።
በወቅቱ ኩባንያው በኢትዮጵያ ያለው የዳታ ዋጋ ከአፍሪካ አማካኝ ዋጋ ጋር ሲነጻጸር በሦስት እጥፍ ያነሰ መሆኑን ጠቁሞ፣ በከፍተኛ ቅናሽ የሚሸጡ ትላልቅ የዳታ ጥቅሎች ኩባንያው ትርፋማ ሆኖ መሠረተ ልማቱን እንዳያሰፋ እንቅፋት እየሆኑበት መሆኑን አመልክቷል።
ሳፋሪኮም እ.ኤ.አ. በ2021 የሥራ ፈቃድ ካገኘ በኋላ፣ በ2022 አገልግሎት በመጀመር ለኢትዮ ቴሌኮም የመጀመሪያው የግል ኦፕሬተር ሆኖ ወደ ገበያው መግባቱ ይታወሳል።
ኩባንያው እስካሁን 300 ቢሊዮን ብር (ከ2.5 ቢሊዮን ዶላር በላይ) ኢንቨስት ያደረገ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት 3,000 የሞባይል ጣቢያዎች አሉት። ይህም የኢትዮጵያን ሕዝብ ግማሽ ያህል ይሸፍናል። ኩባንያው እስከ ታኅሣሥ 2028 (እ.ኤ.አ) ድረስ የጣቢያዎቹን ቁጥር ወደ 6,000 ለማድረስና የሕዝብ ሽፋኑን ከ80 እስከ 90 በመቶ ለማድረስ አቅዷል።
በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ውስጥ ተጨማሪ 500 ቢሊዮን ብር ኢንቨስትመንት እንደሚያስፈልገው ኩባንያው ይገምታል።

በሀገሪቱ እየታየ ያለው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የውጭ ምንዛሬ ለውጥ በኩባንያው የቴክኖሎጂ ግብዓቶች ግዢ እና የኔትወርክ ጥገና ወጪዎች ላይ ጫና ማሳደሩን ተከትሎ፣ አሁን ባለው ዝቅተኛ የዋጋ ሞዴል እንዲህ ያለውን ኢንቨስትመንት መቀጠል አስቸጋሪ እንደሚሆን ተገልጿል።
የሳፋሪኮም ደንበኞች ተደርጓል የተባለው “የዋጋ ማሻሻያ” ሳይሆን “ከፍተኛ ጭማሪ” ነው ሲሉ ለካፒታል ቅሬታቸውን ገልጸዋል። ብዙዎች በተለይም የሳምንታዊ ጥቅሎች የይዘት መጠን በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱ እና ዋጋው መጨመሩ በኑሮአቸው ላይ ጫና እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ወደ ገበያ በገባበት ወቅት በነበረው ዝቅተኛ ዋጋ 12 ሚሊዮን የሚሆኑ ደንበኞችን በአጭር ጊዜ ማፍራት የቻለ ቢሆንም፣ አሁን ላይ የታየው የዋጋ ንረት ግን ደንበኞች ሌሎች አማራጮችን እንዲመለከቱ ሊያደርግ ይችላል የሚል ስጋት አለ። ኩባንያው ገበያው ላይ ያለውን ተወዳዳሪነት ለማስጠበቅ የዋጋ ጭማሪውን በድጋሚ እንዲመለከተውና የተጠቃሚዎችን የኑሮ ውድነት ግምት ውስጥ እንዲያስገባ እየጠየቁ ይገኛሉ።
በሀብት መጠኑ የአፍሪካ ግዙፉ ባንክ የሆነው ስታንዳርድ ባንክ ፣ በኢትዮጵያ ሳፋሪኮም ቴሌኮሙኒኬሽን ውስጥ ለሚደረገው ኢንቨስትመንት አካል የሚሆን የ138 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ድጋፍ ለማቅረብ በኬንያ ግዙፍ የቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢ ከሆነው ሳፋሪኮም ጋር አጋርነት አጋርነት መፍጠሩ ይታወቃል። ይህም ለኩባንያው የዲጅታል መሰረተ ልማት ግንባታ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረዉ ይጠበቃል።
የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ የባለቤትነት መዋቅር በተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ጥምረት የተመሰረተ ሲሆን፣ ከፍተኛውን የባለቤትነት ድርሻ የያዘው በ55.7 በመቶ የኬንያው ሳፋሪኮም (Safaricom Plc) ነው።
የጃፓኑ ግዙፍ ኩባንያ ሱሚቶሞ ኮርፖሬሽን በ27.2 በመቶ ሁለተኛውን ትልቅ ድርሻ ሲይዝ፣ የእንግሊዙ ብሪቲሽ ኢንተርናሽናል ኢንቨስትመንት (BII) ደግሞ 10.9 በመቶ ድርሻ ያለዉ ሲሆን ቀሪው የባለቤትነት ድርሻ በደቡብ አፍሪካው ቮዳኮም ግሩፕ (6.2 በመቶ) እና በዓለም ባንክ ስር በሚገኘው ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን (IFC) የተያዘ መሆኑ ይታወቃል።
እነዚህ አጋር አካላት በጋራ በመሆን ኩባንያው በኢትዮጵያ እያከናወነ ላለው የዲጂታል መሰረተ ልማት ዝርጋታ የፋይናንስና የቴክኒክ ድጋፍ እያቀረቡ ይገኛል።





