ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ከሚያስመዘግቡ አገራት ተርታ ብትሰለፍም፣ በዜጎች የዕለት ተዕለት ኑሮ ላይ የሚታየው እጅግ የከፋ ድህነት ግን በአሳሳቢ ሁኔታ እየጨመረ መሆኑን አዲስ ሪፖርት አመለከተ።
የተባበሩት መንግሥታት የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ጉዳዮች መምሪያ ባወጣው ትንበያ መሠረት፣ ኢትዮጵያ በ2026 የ6.3 በመቶ የኢኮኖሚ ዕድገት ታስመዘግባለች። ይህ ግምት ቀጠናው ካለው የ5.8 በመቶ አማካይ ዕድገት በላይ ቢሆንም፣ የዕድገቱ ፍሬ ግን ወደ ታችኛው የኅብረተሰብ ክፍል እየደረሰ አለመሆኑን ሪፖርቱ አብራርቷል።
የኢትዮጵያ “ዋና ዕድገት” በምስራቅ አፍሪካ ካሉ አገራት መካከል ጠንካራ ከሚባሉት አንዱ ሆኖ ተመዝግቧል። ይህ ዕድገት የተገኘው በተረጋጋ የግብርና ምርታማነት፣ እንደ ወርቅ ባሉ የንግድ ሸቀጦች ላይ በታየ ተመራጭ ዋጋ እና በአገር ውስጥ ፍላጎት መጨመር መሆኑ ተጠቁሟል።
እነዚህ ስኬቶች በዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ ) ፕሮግራሞች ሥር በተተገበሩ ታላላቅ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች የተደገፉ መሆናቸውን ሪፖርቱ አብራርቷል።
ይህ ሁሉ ስኬት ቢመዘገብም፣ ሪፖርቱ በኢትዮጵያ “እጅግ የከፋ ድህነት” እየጨመረ መምጣቱን በማሳሰብ ጥብቅ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል። እንደ ሩዋንዳ እና ቤኒን ያሉ አገራት የኢኮኖሚ ዕድገታቸውን ድህነትን ለመቀነስ ሲጠቀሙበት፣ በኢትዮጵያ ግን የዕድገቱ ፍሬ ወደታችኛው የኅብረተሰብ ክፍል በሚፈለገው ልክ አለመድረሱ ተጠቁሟል።
በተለይም በከተሞች አካባቢ በየዓመቱ የሚታየው የ3.5 በመቶ የሕዝብ ቁጥር ዕድገት በመሠረተ ልማት፣ በቤት እና በመሠረታዊ አገልግሎቶች ላይ ከባድ ጫና ፈጥሯል። ይህም የከተማ ኑሮን ለብዙዎች የማይቀመስ አድርጎታል።
እ.ኤ.አ. በ2025 መገባደጃ ላይ የዓለም አቀፍ የእህል ዋጋ ቢረጋጋም፣ የኢትዮጵያ ዓመታዊ የምግብ ዋጋ ግሽበት ግን ከ10 በመቶ በላይ ሆኖ መቀጠሉን ሪፖርቱ አስታዉሷል። ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት እንደገለፀዉ የታህሳስ ወር አጠቃላይ የዋጋ ንረት ወደ ነጠላ አሃዝ ዝቅ በማለት 9.7 በመቶ ሆኖ ተመዝግቧል።
ካፒታል ጋዜጣ ከተቋሙ ሪፖርት ላይ እንደተመለከተው ፤ አሁን ላይ እየታየ ያለዉ ግሽበት በአገሪቱ እየጨመረ ባለው ፈጣን የከተሞች መስፋፋት ምክንያት ይበልጥ ተባብሷል። በዚህም ወደ ከተሞች የሚደረገው ፍልሰት ሲጨምር፣ ለመኖሪያ ቤትና ለመሠረታዊ አገልግሎቶች ያለው ፍላጎት ከአቅርቦቱ በላይ በመሆኑ የከተማ ኑሮን በጣም ውድ አድርጎታል።
ከዚህ በተጨማሪም ቀልጣፋ ያልሆነ የአቅርቦት ሰንሰለት እና ከፍተኛ የትራንስፖርት ወጪ በከተማ ነዋሪዎች ላይ የምግብ ዋጋ እንዲጨምር ማድረጉ ብቻ ሳይሆን፣ ነዋሪዎቹ የሚመገቡትን የምግብ ዓይነትና መጠን እንዲቀንሱ አስገዳጅ መሆኑ ተገልጿል።
ኢትዮጵያ ካለባት የውጭ ዕዳ ክፍያ ጫና በተጨማሪ፣ ከዓለም አቀፍ ለጋሾች የሚገኘው ይፋዊ የልማት እርዳታ እየቀነሰ መምጣቱ ለሀገሪቱ ተጨማሪ የፋይናንስ ስጋት መፍጠሩ ተገልጿል። ይህም ለልማት መዋል የሚገባው ሀብት ለዕዳ ክፍያ እንዲውል እያደረገው ይገኛል።
ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በአገር አቀፍ የሂሳብ አያያዝ ክለሳ ምክንያት “ጊዜያዊ ያልተመደበ” በሚል ሁኔታ ላይ የምትገኝ ቢሆንም፣ አጠቃላይ የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያዎቿ ግን ለቀጠናው እድገት አዎንታዊ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ።






