👉 የውጭ ምንዛሪ ሂሳብ ለመክፈት ይቀመጥ የነበረው የ100 ዶላር ቅድመ-ሁኔታ ቀርቷል
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ከአለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ጋር የተደረሰውን ስምምነትና የድርጅቱን የአሰራር ደንብ አንቀጽ 8 ድንጋጌዎችን መሠረት በማድረግ፣ በውጭ ምንዛሪ አሰራር ላይ ተጥለው የነበሩ በርካታ የቁጥጥር ቅድመ-ሁኔታዎችንና ክልከላዎችን በከፍተኛ ሁኔታ ማላላቱን አስታወቀ።
ባንኩ ዛሬ የካቲት 4 ቀን 2018 ዓ.ም. እንደገለፀው ፣ ማሻሻያው ከሐምሌ 2016 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ እየተደረገ ያለውን የተሟላ የማክሮ-ኢኮኖሚ ሪፎርም ይበልጥ ለማጎልበትና የውጭ ምንዛሪ ገበያውን ነፃ፣ ግልጽና ቀልጣፋ ለማድረግ ያለመ ነው።
ይህ እርምጃ ኢትዮጵያ ከአይኤምኤፍ የሽግግር ድንጋጌዎች (አንቀጽ 14) በመውጣት፣ ክፍት የሆነ ዓለም አቀፍ የክፍያ ስርዓትን ወደሚያበረታታው አንቀጽ 8 ለመሸጋገር የምታደርገው ጥረት አካል ነው።
በአዲሱ መመሪያ መሠረት ግለሰቦችና ቤተሰቦች በውጭ ምንዛሪ አጠቃቀም ላይ ሰፊ ነፃነት ተሰጥቷቸዋል። ከዛሬ ጀምሮ ማንኛውም የውጭ ምንዛሪ ሂሳብ ያለው ግለሰብ አስፈላጊውን ሕጋዊ ሰነድ በማቅረብ፤ ለትዳር አጋሩና ለልጆቹ የትምህርት፣ የሕክምና እና የጉዞ ወጪዎችን ካለው የውጭ ምንዛሪ ሂሳብ መክፈል ይችላል።
በተጨማሪም ኢትዮጵያውያን በውጭ ሀገር ለሚኖሩ ዘመዶቻቸው እስከ 3,000 የአሜሪካ ዶላር የሚደርስ የገንዘብ ድጋፍ እንዲልኩ የተፈቀደ ሲሆን፣ ቀደም ሲል የውጭ ምንዛሪ ቁጠባ ሂሳብ ለመክፈት እንደ ቅድመ-ሁኔታ ይቀመጥ የነበረው የ100 ዶላር አነስተኛ ተቀማጭ ሙሉ በሙሉ ቀርቷል።
ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ነዋሪዎችም ይዘውት የመጡትን ማንኛውንም የውጭ ምንዛሪ መጠን ያለ ጉምሩክ ሰነድ በባንኮችና በምንዛሪ ቢሮዎች ወደ ብር የመመንዘር ወይም ወደ ውጭ ምንዛሪ ሂሳባቸው የማስገባት መብት ተሰጥቷቸዋል።
የአገልግሎት ዘርፍ ላኪዎችን ለማበረታታት ይረዳ ዘንድ፣ ከሥራቸው የሚያገኙትን የውጭ ምንዛሪ መቶ በመቶ (100%) በሪቴንሽን ሂሳባቸው ውስጥ ያለምንም የጊዜ ገደብ እንዲይዙ ተፈቅዶላቸዋል።
ከዚህ ቀደም ለትርፍ የተቋቋሙ ድርጅቶች ከእርዳታና ከስጦታ የሚያገኙትን የውጭ ምንዛሪ በተለያዩ የሂሳብ አይነቶች (ተንቀሳቃሽ፣ ቁጠባና የጊዜ ገደብ) ማስቀመጥ እንዲችሉ ተደርጓል።
በሌላ በኩል፣ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስተሮች፣ ኤምባሲዎችና ዓለም አቀፍ ተቋማት ያለ ብሔራዊ ባንክ ፈቃድ በንግድ ባንኮች የውጭ ምንዛሪ ሂሳብ መክፈት የሚችሉ ሲሆን፣ የሀገር ውስጥ ድርጅቶችም ኢንቨስትመንታቸውን በብሔራዊ ባንክ እያስመረመሩ ከሀገር ውጭ መዋእለ ነዋያቸውን ማፍሰስ እንዲችሉ መንገድ ተመቻችቷል።
የባንኮች ሚና እና የቴክኖሎጂ አጠቃቀም
የንግድ ባንኮች ለደንበኞቻቸው የውጭ ሀገር ክፍያና የኤሌክትሮኒክ ግብይትን የሚያቀላጥፍ ዓለም አቀፍ የክፍያ ካርድ እንዲያዘጋጁ ፈቃድ ተሰጥቷል።
ባንኮቹ የፎርዋርድ የውጭ ምንዛሪ ግብይትንም ያለ ብሔራዊ ባንክ ማረጋገጫ ማከናወን እንዲችሉ ስልጣን ተሰጥቷቸዋል።
ይህ ሰፊ የማሻሻያ እርምጃ የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሪ ክምችት ለማሳደግ፣ ሕጋዊ የገንዘብ ዝውውርን በማበረታታት ጥቁር ገበያን ለመዋጋትና የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሥርዓት ከዓለም አቀፍ አሰራር ጋር ለማስማማት ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው የብሔራዊ ባንክ መግለጫ ያመለክታል።
ይህ እርምጃ ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ በ2024 የገባችውን ቃል ማለትም የተዘበራረቁ (ባለብዙ) የምንዛሬ ተመኖችን የማስቀረት እና ለወቅታዊ ዓለም አቀፍ ግብይቶች የሚፈጸሙ ክፍያዎች ላይ የሚጣሉ ገደቦችን የማንሳት ቁርጠኝነትን በተግባር ያሳየ መሆኑ ተገልጿል። የአይኤምኤፍ የተራዘመ የብድር አገልግሎት ድጋፍም እነዚህን መሰረታዊ የፖሊሲ ለውጦች በቀጥታ የሚያግዝ መሆኑ ይታወቃል።
በኢያሱ ዘካሪያስ





