በኢትዮጵያ የሚገኙ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችና መንግሥታዊ ተቋማት፣ ለስደተኞች የሚቀርበው ዕርዳታ በአስቸኳይ የገንዘብ ድጋፍ ካልተደገፈ መርሐ-ግብሩ ሙሉ በሙሉ ሊፈራርስ እንደሚችል አስጠነቀቁ።
የኢትዮጵያ ስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ፣ የተባበሩት መንግሥታት ከፍተኛ የስደተኞች ኮሚሽን ( ዩኤን ኤች አር ) እና የዓለም የምግብ ፕሮግራም ባወጡት የጋራ መግለጫ፤ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የሚገኙ ከ1.1 ሚሊዮን በላይ ስደተኞች የሕይወት አድን አገልግሎት መቋረጥ ስጋት ደቅኖባቸዋል።
በአፍሪካ ሁለተኛዋ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ስደተኞች የምታስተናግድ አገር የሆነችው ኢትዮጵያ፣ በሱዳን እና በደቡብ ሱዳን ባለው ግጭት እንዲሁም በሶማሊያ ባለው ድርቅ ምክንያት ከፍተኛ የስደተኞች ፍሰት እያስተናገደች ትገኛለች። ይሁን እንጂ በገንዘብ እጥረት ምክንያት የረድኤት ድርጅቶች በ2025 (እ.ኤ.አ) የሚያቀርቡትን የአደጋ ጊዜ አቅርቦት በ70 በመቶ ለመቀነስ ተገደዋል።
ድርጅቶቹ ለሚቀጥሉት ስድስት ወራት ሥራቸውን ለማስቀጠል 90 ሚሊዮን ዶላር በአስቸኳይ እንደሚፈልጉ ገልጸዋል።
የዓለም የምግብ ፕሮግራም ለ780,000 ስደተኞች የሚሰጠውን ምግብ ከመደበኛው በ60 በመቶ በመቀነስ፣ በቀን ከ1,000 ካሎሪ በታች እንዲያገኙ ለማድረግ ተገድዷል።
በስደተኛ ካምፖች ውስጥ የምግብ እጥረት መጠን ከ15 በመቶ በላይ የጨመረ ሲሆን፣ የሕፃናት የሞት መጠን በ2025 ወደ 4.7 በመቶ ከፍ ብሏል።
የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ጠይባ ሀሰን፣ “ኢትዮጵያ ስደተኞችን የመጠበቅ ግዴታዋን እየተወጣች ነው፣ ነገር ግን ይህ ከባድ ኃላፊነት በመንግሥት ብቻ ሊሸከም የሚችል አይደለም። አቅማችን ተሟጧል፣ እንዲሁም ስደተኞችን በተቀበሉ ማህበረሰቦች ላይ ያለው ጫና ሊቋቋሙት ከሚችሉት በላይ እየሆነ ነው። በዚህ ወሳኝ ወቅት የሰብዓዊ ጥፋትን ለማስወገድ ዓለም አቀፍ ድጋፍ የግድ ያስፈልጋል” ሲሉ የሁኔታውን አሳሳቢነት በግልጽ አሳይተዋል።
የ ዩኤን ኤች አር ተወካይ አይሳቱ ንዳዬ በበኩላቸው፣ የገጠመን ሁኔታ ከዚህ በፊት ታይቶ የማይታወቅ እና እጅግ አሳሳቢ ነው። አሁን የምንወስደው ውሳኔ የኢትዮጵያ የስደተኞች ምላሽ ይፈርሳል ወይስ እንደገና የማገገም እና የዘላቂ መፍትሔዎች ሞዴል ይሆናል የሚለውን ይወስናል” ብለዋል።
ከምግብ በተጨማሪ የውሃ እና የትምህርት አገልግሎቶች ክፉኛ መጎዳታቸውን ካፒታል የተመለከተው መግለጫ ያሳያል።
ስደተኞች በቀን በአማካይ ከ12-14 ሊትር ውሃ ብቻ የሚያገኙ ሲሆን በአንዳንድ አካባቢዎች ይህ ወደ 5 ሊትር ዝቅ ብሏል። ይህም ከአደጋ ጊዜ ዝቅተኛ መመዘኛ (15 ሊትር) በታች መሆኑ ተጠቁሟል።
በሌላ በኩል 110,000 ሕፃናትን የሚያስተምሩ የ57 የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በጀት መቋረጡ የተገለፀ ሲሆን እነዚህ ትምህርት ቤቶች በታህሳስ 22 ቀን 2018 ዓ.ም) እንዲዘጉ ታቅዷል። ይህም መምህራንን ያለ ደመወዝ፣ ተማሪዎችን ደግሞ ያለ ትምህርት ቤት ያስቀራል።
ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸው ሕፃናትን ለጥቃት፣ ለጉልበት ብዝበዛ እና ለሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ተጋላጭ በማድረግ የአንድን ትውልድ ተስፋ አደጋ ላይ እንደሚጥል ሦስቱ ድርጅቶች አሳስበዋል።





