በኢትዮጵያ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሚገኘውን ግዙፉን የኩርሙክ የወርቅ ማዕድን ፕሮጀክት ጨምሮ በአፍሪካ ሦስት ዋና ዋና ይዞታዎች ያሉት አላይድ ጎልድ ኮርፖሬሽን በቻይናው የማዕድን ግዙፍ ዚጂን ጎልድ ለመገዛት ስምምነት ላይ መድረሱን አስታወቀ።
ካፒታል ጋዜጣ ዛሬ ጥር 18 ቀን 2018 ዓ.ም. ከወጣው መረጃ ላይ እንደተመለከተው፣ ዚጂን ጎልድ አላይድ ጎልድን በ5.5 ቢሊዮን የካናዳ ዶላር (በግምት 4 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር) በጥሬ ገንዘብ ለመግዛት የመጨረሻ ስምምነት ተፈራርሟል። ይህ ግብይት በአፍሪካ የማዕድን ዘርፍ በዓመቱ ከተመዘገቡት ትልልቅ ግዥዎች አንዱ ሆኖ ተመዝግቧል።
በሆንግ ኮንግ የአክሲዮን ገበያ የተመዘገበውና የገበያ ዋጋው በግምት 70 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር የሆነው ግዙፉ ዚጂን ጎልድ፣ በዚህ ግዥ አማካኝነት በአፍሪካ ያለውን ተደራሽነት በከፍተኛ ሁኔታ ያጠናክራል ተብሏል።
በስምምነቱ መሠረት ዚጂን ጎልድ ለእያንዳንዱ የአላይድ ጎልድ አክሲዮን 44 የካናዳ ዶላር በጥሬ ገንዘብ የሚከፍል ሲሆን፣ ይህም ኩባንያው ባለፉት 30 ቀናት በገበያ ላይ ከነበረው አማካይ ዋጋ የ27 በመቶ ብልጫ አለው። ይህ ከፍተኛ ዋጋ የቀረበው አላይድ ጎልድ ላለፉት ሁለት ዓመታት ሲያካሂድ የነበረው ስትራቴጂካዊ የንግድ ክለሳ ውጤት መሆኑ ተገልጿል።
የዚጂን ጎልድ ሊቀመንበር ሆንግፉ ሊን እንደገለጹት፣ ይህ ግዥ ኩባንያቸው በአፍሪካ ያለውን ተጽዕኖ በከፍተኛ ሁኔታ ያሳድገዋል። በተለይም በኢትዮጵያ የሚገኘውን የኩርሙክ ወርቅ ፕሮጀክት እና በማሊ የሚገኘውን የሳዲዮላ ፕሮጀክት ለብዙ አሥርተ ዓመታት ምርት የሚሰጡ “የትውልድ ሀብቶች” ሲሉ ጠርተዋቸዋል።
ሊቀመንበሩ አክለውም “እንደ አዲስ ባለቤት፣ በኢትዮጵያ፣ በማሊ እና በኮትዲቩዋር ከሚገኙ ባለድርሻ አካላት ጋር እነዚህን ፕሮጀክቶች የበለጠ ለማሳደግ በጉጉት እንጠብቃለን” ብለዋል።
የአላይድ ጎልድ ሊቀመንበርና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፒተር ማሮን በበኩላቸው፣ “ይህ ግብይት ለአክሲዮን ባለቤቶቻችን ከፍተኛና ፈጣን የጥሬ ገንዘብ ጥቅም የሚያስገኝ ነው” ብለዋል። ግዥው ኩባንያው በአፍሪካ የገነባው ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው የማዕድን ይዞታ ውጤታማ መሆኑን የሚያረጋግጥ እንደሆነም ገልጸዋል።
ግዥው ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ የሚመነዘረው እስከ ሚያዝያ 2026 መጨረሻ ድረስ ይሆናል። ይሁን እንጂ ስምምነቱ እንዲጠናቀቅ የአላይድ ጎልድ ባለአክሲዮኖች በልዩ ስብሰባ በ66.6 በመቶ ድምፅ ግዥውን ማጽደቅ ይኖርባቸዋል።
ከዚህ በተጨማሪም የካናዳ ፍርድ ቤት እና የኢንቨስትመንት ቁጥጥር ተቋማት ፈቃድ ማግኘት እና የኢትዮጵያ፣ የማሊ እና የኮትዲቩዋር መንግስታት እንዲሁም የቻይና የቁጥጥር ተቋማት ይሁንታ እንደሚያስፈልግ ተገልጿል።
ግብይቱ እንደተጠናቀቀ አላይድ ጎልድ በቶሮንቶ እና በኒውዮርክ የአክሲዮን ገበያዎች የነበረው ምዝገባ የሚሰረዝ ሲሆን፣ ኩባንያው ሙሉ በሙሉ በዚጂን ጎልድ ስር ሆኖ ሥራውን ይቀጥላል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግንባታው በመጠናቀቅ ላይ ያለው ኩርሙክ ወርቅ፣ ኢትዮጵያ በወርቅ ልማት የዓለም ካርታን እንደምትቀላቀል ማሳያ ሆኗል። ኩርሙክ ወርቅ ለ12 ዓመታት ወርቅ ማልማት የሚያስችል ክምችት ያለው ሲሆን፣ በዓመት እስከ 9 ቶን በላይ ወርቅ እንደሚያመርት ይጠበቃል።
ከ500 ሚሊዮን ዶላር በላይ ኢንቨስት እየተደረገበት ያለው ይህ ፕሮጀክት በቅርቡ ወደ ማምረት እንደሚገባ ይጠበቃል።




