የገንዘብ ሚኒስቴር የሀገሪቱን የ1 ቢሊዮን ዶላር የዩሮ ቦንድ ዕዳ ለማዋቀር ከግል አበዳሪዎች ኮሚቴ ጋር ደርሶት የነበረውን የመርህ ስምምነት ተግባራዊ እንደማያደርግ በይፋ አስታወቀ።
ጥር 2 ቀን 2026 ዓ.ም የተደረሰው ይህ ስምምነት እንዲቆም የተወሰነው፣ የመንግስታት አበዳሪዎች ኮሚቴ እና ዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት ስምምነቱን መርምረው ካጠናቀቁ በኋላ ነው።
የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ አሰንደገለፁት፤ የስምምነቱ መቋረጥ ዋነኛው ምክንያት “የአበዳሪዎች የእኩልነት መርህ” ካለመከበሩ ጋር የተያያዘ ነው። የመንግስታት አበዳሪዎች ኮሚቴስምምነቱ ከሌሎች ይፋዊ አበዳሪዎች ጋር ከተደረገው የዕዳ ሽግሽግ ማዕቀፍ ጋር እንደማይጣጣም ለኢትዮጵያ መንግስት በደብዳቤ አሳውቋል።
ይህንን ስምምነት ባለበት ሁኔታ ተግባራዊ ማድረግ ሀገሪቱ በሐምሌ ወር 2025 ዓ.ም ከአበዳሪዎች ኮሚቴ ጋር ከፈረመችው የመግባቢያ ሰነድ ጋር የሚቃረን ሆኖ ተገኝቷል።
በተጨማሪም፣ የተደረሰው ስምምነት ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት ጋር ከገባችው የኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ-ግብር ግቦች እና መለኪያዎች ጋር እንደማይጣጣም ተመልክቷል።
ሚኒስቴሩ እንዳለው ከሆነ፣ ስምምነቱን መቀጠል በሀገሪቱ የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋት እና በተመዘገቡ የኢኮኖሚ እድገቶች ላይ ከፍተኛ ስጋት ሊፈጥር ስለሚችል በድጋሚ መደራደር የግድ ሆኗል።
በዚህም መሠረት፣ የኢትዮጵያ መንግስት የዕዳ ሽግሽጉን የፋይናንስ ይዘት በተመለከተ ከግል አበዳሪዎች ኮሚቴ ጋር አዲስ ድርድር ለመጀመር መወሰኑን አስታውቋል።
መንግስት ውይይቱን በድጋሚ መክፈት አስፈላጊ ቢሆንም፣ በሁሉም አበዳሪዎች መካከል ፍትሃዊ የዕዳ ጫና ክፍፍልን የሚያረጋግጥ እና የሀገሪቱን የኢኮኖሚ አቅም ያገናዘበ ዘላቂ መፍትሄ ለማምጣት በቁርጠኝነት እንደሚሰራ ገልጿል።




