የሀገር አቀፍ ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት በመሆን የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አህመድ፣ እንዲሁም በምክትል ፕሬዚዳንትነት አቶ በላይነህ ክንዴ መመረጣቸውን ተከትሎ የንግድና የዘርፍ ማህበራት አዋጅን የተላለፈ ነው የሚል ከፍተኛ የህግ ውዝግብ ተፈጥሯል። እነዚሁ ተመራጭ አመራሮች ከአምስት ወራት በላይ የስልጣን ርክክብ ሳያደርጉ መቆየታቸውም ጉዳዩ ወደ ፍርድ ቤት እንዲያመራ ተጨማሪ ምክንያት መሆኑን ካፒታል ጋዜጣ ያገኘዉ የክስ ሰነድ ያመለክታል።
ይህ ውዝግብ ያተኮረው ባለፈው መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም. በተካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ሲሆን፤ አዲሱ አመራር በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አዲስ በወጡ መመሪያዎች መሰረት ስልጣን እንዲረከብ ተደርጓል። በቀጥታ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የወጡት አዲሶቹ ደንቦች፣ ዕጩዎች ቢያንስ አንድ ቢሊዮን ብር የተመዘገበ ካፒታል እንዲኖራቸው እና ቢያንስ ሁለት ሥራ ላይ ያሉ የማምረቻ ፋብሪካዎችን እንዲያስተዳድሩ ግዴታ ይጥላሉ። ይህ አሰራር ትናንሽ እና መካከለኛ አምራቾችን ከውድድር ውጭ እንደሚያደርግላቸው የቀድሞ አመራሮች ይከራከራሉ።
የቀድሞው የምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚዳንት እና ኋላም የፕሬዚዳንቱን ቦታ ተክተው ላለፉት አምስት ዓመታት ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ አበባየሁ ግርማ፤ ከኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት ተወካይ ወዩማ ገሜሳ እና ሌሎች ከሳሾች ጋር በመሆን ውጤቱን ውድቅ እንዲያደርግላቸው ለፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ንግድ እና ኢንቨስትመንት ፍርድ ቤት ክስ መስርተዋል።
ከሳሾቹ እንደሚያብራሩት፣ አዲሱ የገንዘብ ገደብ መስፈርት የንግድና የዘርፍ ማህበራትን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 341 በቀጥታ የሚቃረን ነው። አዋጁ የተዘጋጀው ትላልቅ ኮርፖሬሽኖች አመራሩን እንዲቆጣጠሩት ሳይሆን፣ በሁሉም ክልሎች የሚገኙ ትናንሽ እና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ድርጅቶችን ድምፅ ለማሰማት ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን ይገልጻሉ።
“ይህ የንግድ ምክር ቤት ሳይሆን የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ነው” ያሉት አቶ አበባየሁ፣ አዲሱ መስፈርት አነስተኛ የማምረቻ አቅም ያላቸውን ክልላዊ አምራቾች ሆን ብሎ ማግለሉን ተችተዋል። መስራቾቹም ባለፉት 16 ዓመታት ውስጥ በነበረው መሠረታዊ ማዕቀፍ ውስጥ ከሠሩ በኋላ፣ እንዲህ ዓይነት መስፈርቶች በድንገት መተግበራቸውን መቀበል እንዳከበዳቸው አንስተዋል።
ከዚህ በተጨማሪም ክሱ፣ ምርጫውን የሚመራውን ህጋዊ ማዕቀፍ የጣሰ መሆኑን ይከራከራል። በሥራ ላይ ባለው አዋጅ መሠረት ማንኛውም ግለሰብ በፕሬዚዳንት ወይም በምክትል ፕሬዚዳንትነት ለመወዳደር አስቀድሞ በየክልሉ ምክር ቤት ቦርድ አባል ሆኖ ማገልገል እንዳለበት ይደነግጋል። ይሁን እንጂ የቅርብ ጊዜው ምርጫ የሚኒስቴር መመሪያዎችን በመጠቀም በተሾሙ ግለሰቦች አማካኝነት የክልል አምራች ተወካዮችን ማለፉን ያብራራሉ።
እንደ ከሳሾቹ ገለጻ፣ አዲሶቹ አመራሮች ከተመረጡ ከአምስት ወራት በላይ ያስቆጠሩ ቢሆንም እስካሁን የስልጣን ርክክብ አላደረጉም፤ ይህም ሌላኛው ፍርድ ቤት እንዲታይላቸው የጠየቁት ጉዳይ ነው። በባህላዊ አሰራር ርክክብ የሚደረገው ምርጫው ከተጠናቀቀ ከጥቂት ቀናት ውስጥ ሲሆን፤ ይህም ድርጅታዊ ንብረቶችን ለመጠበቅ እና የተጀመሩ ሥራዎችን ለማስቀጠል ወሳኝ መሆኑን አቶ አበባየሁ አፅንኦት ሰጥተዋል።
የቀድሞው አመራሮች ከአዲሶቹ ተመራጮች ጋር ግንኙነት ለመፍጠር ያደረጓቸው ተደጋጋሚ ሙከራዎች ምላሽ እንዳገኙ ቢገልጹም፣ ለአዲሱ አመራር ቅርብ የሆኑ ምንጮች ግን አመራሮቹ የተቋሙን ሥራዎች አጠቃላይ ጥናት ለማድረግ ርክክቡን ማዘግየታቸውን ለካፒታል ተናግረዋል። ከሳሾቹ በበኩላቸው ይህንን ምክንያት አልተቀበሉትም።
“ምን መረጃ እንዳለ ሳያወቁ እንዴት ቢሮን ኦዲት ማድረግ ይችላሉ?” ሲሉ የሚጠይቁት አቶ አበባየሁ፣ የተቋም አባልነት አገልግሎቶች እና የኢንዱስትሪ ድጋፎች በኦዲት ስም መቋረጥ የለባቸውም ብለዋል።
የዚህ የህግ ውዝግብ ውጤት የኢትዮጵያ ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት አባላት ለሆኑት አጠቃላይ የማኑፋክቸሪንግ ሴክተር፣ በተለይም ለአነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ትልቅ ፋይዳ አለው። ካፒታል ከኢትዮጵያ ኢንተርፕራይዝ ልማት ባገኘው መረጃ መሠረት፣ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ 4 ሺህ 177 የተመዘገቡ መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞች የሚገኙ ሲሆን፤ በመላ ሀገሪቱ ባሉ አነስተኛ እና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ከ25 ሺህ በላይ አጠቃላይ ኢንተርፕራይዞች ተመዝግበው ይገኛሉ።





